በወቅታዊ የሀገራችን ሁኔታ ላይ ከሰመጉ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ በአገሪቱ በአንዳንድ አካባቢዎች በተለያዩ ምክንያቶች እየተቀሰቀሱ ያሉ ግጭቶች ዘላቂ መፍትሄ ይፈለግላቸው!

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ በሀገራችን የተለያዩ አካባቢዎች ለሚከሰቱ በተለይም ከማንነት ጋር የተያያዙ ግጭቶችና ጥቃቶች ዘላቂና የማያዳግም መፍትሄ እንዲሰጣቸው፤ እንዲሁም በግጭቶቹ እና በጥቃቶቹ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ እጃቸው ያለበት አካላት በህግ ተጠያቂ እንዲደረጉ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ሲያሳስብና ሲጠይቅ መቆየቱ ይታወሳል። ይሁንና ግጭቶቹና ጥቃቶቹ በተለያዩ አካባቢዎች ተባብሰው እየቀጠሉ እንደሚገኙ ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ለሰመጉ የሚቀርቡ አቤቱታዎችና ሪፖርቶች ያመላክታሉ። ከጥቅምትና ህዳር ወር 2011 ዓም ጀምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሰው ህይወት መጥፋት፣ የአካል ጉዳት፣ የንብረት መውደም፣ መፈናቀልና የተለያዩ ጉዳቶች ተፈፅመዋል፤ አሁንም እየተፈፀሙ ይገኛሉ። ከዚህ በታች የተዘረዘሩትም ይህንን ያመላክታሉ፤

  • በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ቦረና ዞን ሞያሌ ከተማ በገሪና ቦረና ጎሳዎች መካከል ባለው ግጭት ከህዳር ወር መጀመሪያ ጀምሮ ከ50
    በላይ የሰዎች ህይዎት ጠፍቷል፣ ከፍተኛ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመትም ደርሷል። ከዚህ በተጨማሪ ታህሳስ 8 ቀን 2011 ዓ.ም ሞያሌ
    ከተማ በቀለ ሞላ ሆቴል ውስጥ በታጣቂዎች በተፈፀመ ጥቃት የ12 ሰዎች ህይዎት ጠፍቷል። በነቀምቴ፣ በነጆ፣ ጋሆ ቄቤ፣ በሀሮ ሊሙ
    በሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች በተፈፀሙ ጥቃቶች ከ30 በላይ ሰዎች ህይወት የጠፋ ሲሆን አንድ ሰው ቆስሏል። መንግስት በአካባቢው የሚገኙ የኦነግ
    ታጣቂዎች ድርጊቱን እንደፈፀሙት ቢያመላክትም እስካሁን ማረጋገጫ አልተገኘለትም። በ17/04/2011 ዓ.ም የጊቶ ጊዳ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪናየግብርና ፅ/ቤት ሀላፊ ባልታወቀ አካል በነቀምቴ ከተማ ውስጥ ተገድለዋል። በዚሁ እለት በነቀምቴ ከተማ በመንግስት የፀጥታ ሀይሎች 2 ሰዎች ተገድለዋል።
  • በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ምዕራብ ጎንደር ዞን ከህዳር 22 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ በጭልጋና በደንቢያ አካባቢዎች በአማራና በቅማንት
    ማህበረሰብ መካከል በተነሳ ግጭት ቢያንስ የ50 ዜጐች ህይወት አልፏል፣ ከፍተኛ የሆነ ንብረት መውደምና ቃጠሎ ደርሷል፣ ዘረፋና ማፈናቀል
    ተፈፅሟል። በአሁኑ ሰዓትም ከፍተኛ የጸጥታ ችግር ያለ ሲሆን የክልሉ መንግስት ችግሩን ለመፍታት ወንጀለኞችን በህግ ቁጥጥር ስር እያዋለ
    እንደሚገኝ ከአካባቢው ለሰመጉ የደረሱት መረጃዎች ያመላክታሉ።
  • ሲዳማ ዞን በንሳና ቦና ወረዳዎች “መሬታችን ለኢንቬስተር አላግባብ ተሰጥቷል” በሚል ምክንያት የተፈጠረ አለመግባባት በወረዳው ካቢኔ
    አንመራም ወደሚል ተቃውሞ ተሸጋግሮ ከህዳር ወር አጋማሽ ጀምሮ በተቃውሞ ላይ የነበሩ 29 የሀገር ሽማግሌዎች በበንሳ ፖሊስ ጣቢያታስረው
    ይገኛሉ፤ በዞኑ በሊላ ወረዳ ከምዕራብ ጉጅ ዞን በሚያዋስን ድንበር ላይ ከህዳር ወር ጀምሮ በተፈጸመ ጥቃትና ግጭት ከ25 እስከ 35 የሚገመት
    የሰው ህይዎት መጥፋቱን፤ በሚሊዮን ብር የሚገመት የግልና የመንግስት ንብረት መውደሙን የሰመጉ ምንጮች ገልፀዋል።
  • በምዕራብ ጉጂ ዞንና በደቡብ ክልል ቡርጂ ወረዳ ከ03/04/2011ዓ.ም ጀምሮ በታጠቁ ኃይሎች በተፈፀመ ጥቃት የ13 ሰዎች ሕይወት ጠፍቷል፤
    የአካል ጉዳት ደርሷል፤ ግምቱ ያልታወቀ ንብረት ተዘርፏል፤
  • በጉራጌ ዞን በመስቃንና ማረቆ ማህበረሰብ መካከል ከመስከረም 03 ቀን 2011 ዓም ጀምሮ በተፈፀሙ ግጭቶች ቁጥራቸው ከ50 (ሃምሳ) በላይ
    ዜጐች ህይወት ጠፍቷል፣ በሰው አካል እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል፤ በርካታ ዜጐችም ከመኖሪያ ቀያቸው ተሰደዋል። ከችግሩ ጋር
    በተያያዘ የሁለቱም ወረዳ አስተዳዳሪዎችና የመንግስት ሰራተኞች በቁጥጥር ስር ዉለው ምርመራ እየተደረገባቸው ይገኛል።
  • የራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ ያነሱ ዜጐች በጥቅምት ወር መጀመሪያ ጀምሮ ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣታቸው ምክንያት የ5 ዜጐች ህይወት ማለፉን
    ገልፆ ሰመጉ ጋዜጣዊ መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል። ከዚሁ የራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ ከጥቅምት ወር ጀምሮ 761 የማህበረሰቡ
    ተወላጆች መቀሌ፣ ማይጨው፣ ውቅሮ፣ ተንቤን ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ እስር ቤቶች ታስረው እንደሚገኙ የራያ የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ
    ኮሚቴ ለሰመጉ ገልጿል፤
  • በደቡብ ክልል አማሮ ኬሌ ወረዳ በአማሮና በጉጂ መካከል ከሁለት አመት በላይ በቀጠለ ግጭት በርካታ ሰዎች ተገድለዋል፣ ቤት ንብረታቸው
    ወድሟል። በ10/04/2011 ዓ.ም የአማሮ አርሶ አደሮች ንብረት የሆኑ 156 ከብቶች በጉጂዎች በመወሰዳቸው ግጭት ተቀስቅሶ የአማሮ ኬሌ ተወላጅ
    የሆነ አንድ አርሶ አደር ህይወት ማለፉን ሰመጉ አረጋግጧል፤
  • ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በያሶን ወረዳ ይኖሩ የነበሩ ቁጥራቸው 1,200 የሚሆኑ የአማራ ብሄር ተወላጆች ተፈናቅለው ከህዳር 15 ቀን 2011 ዓም
    ጀምሮ ባህርዳር ከተማ ዘን ዘልማ በሚገኝ የገበያ ማዕከል ተጠልለው ይገኛሉ፤
  • በቦረና ዞን ተልተሌ ወረዳ በሚኖሩ የቡርጂና ኮንሶ ተወላጆች ታህሳስ 10 ቀን 2011 ዓ.ም በቦረና ተወላጆች መኖሪያ ቤቶቻቸው ተቃጥሎ
    አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል። ተፈናቃዮቹም ጃርሶ ቀበሌ ተጠልለው ቢገኙም፤ ከዚህም ቦታ ለቀው እንዲሄዱ የተለያዩ ጫናዎች
    እየተደረገባቸው መሆኑን ከአካባቢው ለሰመጉ የደረሱት መረጃዎች ያመላክታሉ፤
  • ጥቅምት 18 ቀን 2011 ዓ.ም በድሬዳዋ ከተማ በገንደ ገራዳ፣ ገንዳ ቦዬ እንዲሁም ገንደ ተስፋ የተባሉ አካባቢዎች ከህገ ወጥ የመሬት ወረራና
    እንዲሁም ከጸጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ ግጭት ፖሊስም ሁኔታውን ለማረጋጋት በወሰደው እርምጃ የሁለት ሰዎች ህይዎት አልፏል። 6 ሰዎች
    ጉዳት ደርሶባቸው በድል ጮራ ሆስፒታል ህክምና ላይ ይገኛሉ፤
  • ጥቅምት 21 ቀን 2011 ዓ.ም ድሬዳዋ ዙሪያ ቢራ የሚባል ቀበሌ 1 ማህበር በኦሮሞና በሱማሌ ጎሳዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት 12 የሚሆኑ ቤቶች
    መቃጠላቸውን፣ እንዲሁም 4 ሰዎች በጥይት ተመተው ቆስለው በህክምና ላይ ይገኛሉ፤
  • ታህሳስ 13/2011 ዓ.ም ጀምሮ በምስራቅ ኢትዮጵያ በሱማሌ ክልልና በኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ በሆኑት ሲቲ ዞንና ምስራቅ ሃራርጌ ዞን የረር ጎታ
    በሚባል አካባቢ ብሄርን መሰረት ያደረገ ግጭት ተከሰቶ የ5 ሰዎች ህይወት አልፏል፤
  • በቡሌ ሆራ ዩንቨርሲቲ ከታህሳስ 4 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ ከአማራ ክልል የመጡ ተማሪዎችን በገጀራ፣ በጩቤና በፌሮ ብረት በማስፈራራትና
    ድብደባ በመፈፀም ተማሪዎቹ ከማደሪያቸው መውጣታቸውን፣ አንድ ተማሪም ከሦስተኛ ፎቅ ወድቆ በደረሰበት ጉዳት ሆስፒታል ገብቷል። ወደ
    ቤተሰቦቻቸው ለመመለስ እንደተከለከሉ የገለጹት ተማሪዎች ወደ ማደሪያቸውም ለመመለስ ያልቻሉ ሲሆን በዩንቨርሲቲው ግቢ ውስጥ
    በመከላከያ ተከበው ጥበቃ እየተደረገላቸው ቆይተዋል። ችግሩን ለመቅረፍ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት ቢደረግም ተማሪዎች
    ለደህንነታቸው ስጋት እንዳላቸው በመግለፅ ለ12 ቀናት ሜዳ ላይ ውለው ካደሩ በኋላ ዩኒቨርሲቲውን ለቀው ወደየቤተሰቦቻቸው ተመልሰዋል።
    ግቢውን ለቀው ከመውጣታቸው በፊትም በተደራጁ ኃይሎች በድንጋይ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው እና ከ10 በላይ ተማሪዎች በደረሰባቸው
    ጉዳት ለህክምና መወሰዳቸውን ሰመጉ አረጋግጧል።
  • የወለጋ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በነቀምቴ፣ በነጆ፣ ጋሆ ቄቤ፣ በሀሮ ሊሙ በ03/03/2011 ዓ.ም ለሞቱ ዜጎች ሀዘናቸውን ለመግለጽ በ25/03/2011
    ዓ.ም በወጡበት ወቅት 15 ዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች በታጠቁ የመንግስት ኃይሎች በጥይት ተመተው አንዱ ህይወቱ ሲያልፍ 13 ሆስፒታል
    ታክመው ወጥተዋል። አንድ ተማሪ በነቀምቴ ሪፈራል ሆስፒታል ተኝቶ ህክምናውን እየተከታተለ ይገኛል።
  • ጅማ፣ አምቦ፣ ደብረ ብርሃን፣ ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲዎች፤ እንዲሁም በሀዋሳ ከተማ አዲስ ከተማ መሠናዶ ትምህርት ቤት በተማሪዎች መካከል
    ብሔርን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች ተቀስቅሰው ተማሪዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ የመማር ማስተማር ሒደቱም በተለያየ ወቅት ተቋርጦ ቆይቷል።

ማጠቃለያ

በአጠቃላይ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች በተለያዩ ምክንያቶች በተለይም ከማንነት ጋር በተያያዘ ግጭቶች እየተባባሱ የበርካታ
ዜጎችን ህይወትና ንብረትን እያጠፋና ለዘመናት ከኖሩበት መኖሪያ ቀያቸው እያፈናቀለ ይገኛል። በተመሳሳይ ምክንያቶች በበርካታ ዩኒቨርሲቲዎች
ከማንነት ጋር በተያያዘ የሚነሱ ግጭቶች የተማሪዎችን ህይወት መጥፋት፣ አካላዊ እና ስነልቦናዊ ጉዳት እያስከተሉ ሲሆነ የመማር ማስተማሩ ሂደት
በበርካታ ዩኒቨርሲቲዎች እየተስተጓጎለ ይገኛል። እንዲሁም ብሄርን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች እንደቀጠሉ ለሰመጉ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚደርሱት
መረጃዎች ያመላክታሉ። እየተባባሱ የመጡት ሁኔታዎች ሀገሪቱ እየተጓዘችበት ያለውን የለውጥ መንገድ ከማስተጓጐልም አልፎ አስከፊ ወደሆነ የእርስ
በርስ ግጭት ሊወስድ የሚችል እንደሆነ እየታየ ነው። ለግጭቶቹ መባባስ እና እየደረሰ ላለው ሰብዓዊ እና ቁሳዊ ውድመት በተለያዩ የሀገራችን
አካባቢዎች በስፋት እየተዘዋወረ ያለው ህገወጥ የጦር መሳሪያ እና ከህግ አግባብ ውጪ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ዜጐች ከፍተኛውን ሚና እየተጫወቱ
ይገኛሉ። ላለፉት አመታት የመንግስት ታጣቂ ኃይሎች ይወስዱት የነበረው ያልተመጣጠነ የሃይል እርምጃ ጋብ ባለበት በዚህ ወቅት፤ በተለያዩ የሀገሪቱ
ክፍሎች ከህግ አግባብ ውጪ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች በየቦታው ለሚታዩት ግጭቶች እና ውጥረቶች ምክንያቶች ሆነዋል።

በአንፃሩ መንግስት በዜጐች መካከል እየተባባሱ የመጡትን ብሔር-ተኮር ግጭቶች እና ጥቃቶች ሳይፈፀሙ ቀድሞ በመከላከል በኩልም ሆነ፤ ችግሮቹ
ከተፈጠሩ በኋላ በፍጥነት ተቆጣጥሮ የጉዳት መጠኑን ለመቀነስ እያደረገ ያለው ጥረት የችግሩን ስፋትና ጥልቀት የሚመጥን ሆኖ አልታየም። የዜጐችን
በሕይወት የመኖር መብት፣ የአካል ደህንነት መብት፣ በማንኛውን የሀገሪቱ ክፍል ያለገደብ ተንቀሳቅሶ የመኖር፣ የመስራት እና ንብረት የማፍራት ህገ
መንግስታዊ መብትን በመጠበቅ እና በማስከበር ረገድ ከፍተኛ ጉድለት ታይቶበታል። መንግስት በህገወጥ መንገድ ወደ ሀገሪቱ እየገባ ያለውን ቁጥሩ
ከፍተኛ የሆነ የጦር መሳሪይ ዝውውር በመቆጣጠር፣ የጦር መሳሪያውን ምንጭ በመግታት፣ ከህግ አግባብ ውጪ የጦር መሳሪያ በታጠቁ ሰዎች ላይ
ጥብቅ ክትትል በማድረግ እና ትጥቅ በማስፈታት በኩልም በሚጠበቅበት ደረጃ ሲንቀሳቀስ አልታየም። ግጭትን ቀስቃሽ ንግግሮች እና ማነሳሳቶች
በተለያዩ አካላት ሲፈፀሙም መቆጣጠር አልቻለም።

በሀገሪቱ በበርካታ አካባቢዎች እነዚህና ሌሎች ተመሳሳይ ግጭቶችና ጥቃቶች ለአመታት መንግስት ሲከተለው የነበረው ብሔርን እና ቋንቋን መሠረት
ያደረገ ፖለቲካ ውጤት መሆኑ አያጠያይቅም። መንግስት ብሔርን እና ቋንቋን መሠረት ያደረገውን የፌዴራል አደረጃጀት ክፍተቶች እና ችግሮች
በመመርመር ተገቢውን ማስተካከያ እንዲያደርግ ሰመጉ በተደጋጋሚ ሲጠይቅ መቆየቱ ይታወሳል፤ አሁንም በድጋሚ ይጠይቃል።

በመጨረሻም በተለያዩ አካባቢዎችና በዩኒቨርስቲዎች ውስጥ ዜጎች በሰላምና በመግባባት እንዳይኖሩ እንዲሁም ግጭቶችን በመቀስቀስ ለበርካቶች
ህይወት መጥፋት፣ የአካል ጉዳት፣ የንብረት መውደምና መፈናቀል በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸው ያለባቸውን አጣርቶ በመለየት በህግ አግባብ
ተጠያቂ እንዲደረጉ፤ ለተጐጂዎች እና ቤተሰቦቻቸው ተመጣጣኝ ካሳ እንዲከፍል፤ በግጭቶቹ እና በደህንነት ስጋት ምክንያት ትምህርታቸውን ያቋረጡ
የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ አስፈላጊው ጥበቃ እንዲደረግላቸው ሰመጉ ጥሪውን ያስተላልፋል። በተጨማሪም
መንግስት በተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩ ግጭቶችን በረጋ እና በሰከነ መንፈስ ችግሮችን ከመነሻው በማጥናት፤ ለዜጐች ደህንነት እና ለሀገር አንድነት
ቅድሚያ በመስጠት የሚመለከታቸውን የህብረተሰቡ ክፍሎች ያሳተፈ መፍትሔ እንዲፈልግ ሰመጉ በድጋሚ ይጠይቃል። በግጭቱ ተሳታፊ የሆኑ
ወገኖችም ሠላም በጠመንጃ አፈሙዝ እንደማይመጣ አምነው በመቀበል ልዩነቶቻቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ ለመፍታት ከመንግስት ጋር ተቀራርበው
እንዲሰሩ ሰመጉ ይጠይቃል።

መግለጫውን በፒዲኤፍ እዚህ ያገኛሉ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

*

*

*