ሰመጉን ይደግፉ ለሰብዓዊ መብች መከበር የበኩልዎን አስተዋጽዖ ያበርክቱ

hrco-fund-raising-events-20

ሰመጉን ይደግፉ ለሰብዓዊ መብች መከበር የበኩልዎን አስተዋጽዖ ያበርክቱ

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) በኢትዮጵያ የሽግግር ወቅት ቻርተር አንቀጽ 1(ሀ) እና በኢትዮጵያ ፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር ከ404–482 በተጻፉት ድንጋጌዎች መሠረት መስከረም 29 ቀን 1984 ዓ.ም. በአባላት የተመሠረተ ማኅበር ነው፡፡ ሰመጉ በበጎ አድራጎትና ማኅበራት ዐዋጅ ቁጥር 621/2001 መሠረት “ኢትዮጵያዊ የበጎ አድራጎት ማኅበር” ሆኖ በምዝገባ ቁጥር 1146 በሕጋዊነት የሚንቀሳቀስ፣ ከማናቸውም የፖለቲካ ፓርቲና ድርጅት የማይወግን፣ ለትርፍ ያልተቋቋመ፣ ነጻና ገለልተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብቶች ተከላካይ ተቋም ነው፡፡ ሰመጉ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መጎልበት፣ ለሕግ የበላይነት መስፈንና ለሰብዓዊ መብቶች መከበር የቆመ ድርጅት ነው፡፡

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ ላለፉት ሁለት ዐሥርታት የሰብዓዊ መብቶች ማስከበር ሥራውን ሲያከናውን የቆየው ከአባላት፣ ከደጋፊዎች፣ በሐገር ውስጥና በውጭ ሐገር ከሚገኙ በጎ አድራጊ ግለሰቦችና ድርጅቶች እንዲሁም ከውጭ መንግሥታት በሚያገኘው እርዳታና ድጋፍ ነበር፡፡ ነገር ግን በ2001 የወጣው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማሕበራት ዐዋጅ እንደ ሌሎች መሰል ድርጅቶች ሁሉ ሰመጉም ከጠቅላላ በጀቱ ከ10 በመቶ በላይ ከውጭ ምንጮች እንዳያገኝ ስለሚከለክልና የበጀቱን 90 በመቶ ከሐገር ውስጥ ምንጮች እንዲሰበስብ ስለሚያስገድድ፣ ይህም አዳጋች ሆኖ ስለተገኘ ለሰመጉ የሰብዓዊ መብት ሥራዎች መዳከም ዋነኛ ምክንያት ሆኖ ቆይቶአል፡፡

የአባላት ድርጅት የሆነው ሰመጉ ከአባላት በሚሰበስበው ወርኃዊ መዋጮ ብቻ የሰብዓዊ መብቶች ማስከበር ሥራውን በመላው ኢትዮጵያ በአጥጋቢ ሁኔታ ለማከናወን ተስኖት የቆየ ሲሆን፣ ይህን ችግር ለመቅረፍ ይችል ዘንድ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ነድፎ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡

የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብሮቹም የሚከተሉት ናቸው፡-

  1. በአነስተኛ ዋጋ የሚሸጡ ስቲከሮችን፣
  2. የተለያዩ ቀለም ያላቸውን ቲሸርቶችን፣
  3. በጨረታ የሚሸጡ የተለያዩ ስዕሎች እንዲሁም
  4. የምሳ ዝግጅት እሑድ ጥቅምት 13 2009 ዓ.ም በደሳለኝ ሆቴል አዘጋጅቷል

ስለሆነም በዚህ የምሳ ዝግጅት ላይ የመግቢያ ካርድ እንዲሁም ከላይ ለሽያጭ የቀረቡትን ቲሸርቶችና ስቲከሮችን በመግዛት ለሰብዓዊ መብቶች መከበር የበኩላችሁን እገዛ እንድታደርጉ ሰመጉ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ሁሉም መብቶች ለሁሉም!

 

ስቲከሮች፣ ቲሸርቶችና የምሳ ዝግጅት መግቢያ ካርድ የሚገኝበት ቦታ፡

የሰመጉ ዋናው መሥሪያ ቤት በሚገኝበት (አዲስ አበባ ስታዲየም ሣኅለ ሥላሴ ሕንፃ 8ኛ ፎቅ፤

ቢሮ ቁጥር 19)

ስልክ ቁጥር ቢሮ +251 115 58 23 87

+251 118 68 57 06

ሞባይል  0912 112580

0911 456032

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

*

*

*