Latest Posts

ሰመጉ በመንግስት የታገደበት በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ እንዲለቀቅለት ጠቅላይ ሚንስቴር ፅ/ቤትን በደብዳቤ ጠየቀ።

የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ከህግ አግባብ ውጭ በ2002 ዓ.ም በኢፌድሪ በጎ አድራጎትና ማህበራት ኤጀንሲ በተፃፈ ደብዳቤ የታገደበትን ስምንት ሚሊዮን ሰባት መቶ ዘጠና ሰባት ሺ አንድ መቶ ሰማንያ አራት ብር እንዲለቀቅለት ለጠቅላይ ሚንስቴር ፅ/ ቤት ደብዳቤ አስገባ።

ለጠቅላየ ሚንስቴር ፅ/ቤት የተፃፈ ደብዳቤ በፒዲኤፍ

 

የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈፃሚዎች ላይ መንግስት በመውሰድ ላይ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል!!

ሕዳር 04 ቀን 2011 ዓ.ም.

የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ሰኞ ሕዳር 03 ቀን 2011 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ በአዲስ አበባ ውስጥ ብቻ አሰቃቂ ድርጊት የሚፈጸምባቸው 7 ድብቅ እስር ቤቶች መገኘታቸውን፤ ከእነዚህም በተጨማሪ በማረሚያ ቤቶችና በፖሊስ ጣቢያዎችም ጭምር በተጠረጣሪዎች ላይ ከሰብዓዊነት ያፈነገጠ እጅግ አሰቃቂ ድርጊቶች ሲፈፀሙ መቆየታቸውን ገልፀዋል። ከእነዚህ በህግ ጥላ ስር በሚገኙ ዜጐች ላይ ከሚፈፀሙት የማሰቃየት ድርጊቶች መካከልም የታሳሪዎችን ሰውነት በኤሌክትሪክ ሾክ ከማድረግ ጀምሮ ብልት ላይ ውሃ የያዘ የፕላስቲክ ኮዳ ማንጠልጠል፣ብልትን በፒንሳ መሳብ፣ ጥፍር መንቀል፣ ከአውሬ ጋር ማሳደር፣ ሴቶች ታሳሪዎችን መድፈር፣ በወንዶች ላይ ግብረሰዶም መፈፀም፣ እንዲሁም ደብዛን ማጥፋት በጉልህ የሚጠቀሱ በሕግ ጥላ ስር በተገኙ ዜጐች ላይ የተፈፀሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች መሆናቸውን ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ አረጋግጠዋል።

ኢሰመጉ (ሰመጉ) ባለፉት 27 አመታት ይህ ድርጊት በተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፤ ሃሳብን የመግለፅ ሕገመንግስታዊ መብታቸውን ተጠቅመው ሃሳባቸውን በነፃነት ሲያንሸራሽሩ በነበሩ ጋዜጠኞች እና አክቲቪስቶች፣ እንዲሁም የሲቪል ማህበረሰቡ አባላት ላይ እየተፈፀመ መሆኑን በማጋለጥ መንግስት የእርምት እርምጃ እንዲወስድ ሲወተውት መቆየቱ ይታወሳል፡፡ መንግስት ለአመታት ለችግሩ ምላሽ መንፈግ ብቻ ሳይሆን የማሰቃየት ድርጊቶቹን ውጤት በመጠቀም የዜጐችን ሕገመንግስታዊ እና ሠላማዊ ጥያቄዎች በሃይል ሲያዳፍን ብሎም ንፁሐንን ሲያሸብር ቆይቷል፡፡ ይህንንም የማሸበር ድርጊት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በህዝብ ተወካዮች ፊት በመቅረብ በግልፅ መናገራቸው እና ይቅርታ መጠየቃቸው የሚታወስ ነው፡፡ እነዚህ የማሰቃየት ድርጊቶች ለዜጐች ከለላ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቅ ከነበረው ፍርድ ቤት የተደበቀ እንዳልሆነ በፍርድ ቤቶች ውስጥ የማሰቃየት ድርጊት ሰለባዎች ለችሎት ከሚያቀርቡት የቃል እና የፅሁፍ አቤቱታዎች በተጨማሪ፤ ልብሶቻቸውን በድፍረት በማውለቅ አካላዊ ጉዳታቸውን ቢያሳዩም በፍርድ ቤቶች በኩል የተወሰዱ እርምጃዎች አለመኖራቸው ታይቷል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቶች የዜጐችን ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የማስከበር ግዴታቸውን በአግባቡ ባለመወጣታቸው ዜጐች እምነት አጥተውበት ቆይተዋል፡፡

ባለፉት 7 ወራት የመጣውን የመንግስት አስተዳደር ለውጥ ተከትሎ በመንግስት በኩል ሲወሰዱ የነበሩት እርምጃዎች በመልካምነታቸው የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ በተለይም ላለፉት 27 አመታት መንግስታዊ ሃላፊነትን ተገን በማድርግ በንፁሃን ላይ ኢሰብዓዊ ድርጊቶችን ሲፈፅሙ በቆዩ የብሔራዊ ደህንነት የስራ ኃላፊዎች እና ድርጊቱን በቀጥታ ሲፈፅሙ በነበሩ ግለሰቦች ላይ እየተወሰደ ያለው ህጋዊ እርምጃ የሚደገፍ ነው፡፡ እስካሁን ከተወሰደው የማጣራት ስራ በተጨማሪም ተመሳሳይ ድርጊቶችን ሲፈፅሙ እና ሲያስፈፅሙ የነበሩ ሌሎች የመንግስት ኃላፊዎችም ላይ እርምጃው እንዲቀጥል ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ መንግስት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ፈፃሚዎች ላይ መውሰድ የጀመረውን ሕጋዊ እርምጃ በመደገፍ ረገድ፤ ከሰብዓዊ መብት ጥሰቱ ሰለባዎች ያሰባሰባቸውን መረጃዎች ለሚመለከተው የህግ አስከባሪ አካል መስጠትን ጨምሮ በማናቸውም መንገድ የሚጠበቅበትን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡ በተጨማሪም የማሰቃየት ድርጊቶቹ ሰለባ የሆኑ ዜጐች የደረሰባቸው አካላዊ ብቻ ሳይሆን ስነልቦናዊ እና ማህበራዊ ጉዳት በቀላሉ የሚሽር እንዳልሆነ እሙን ነው። በመሆኑም ለተጐጂዎችና ለቤተሰቦቻቸው ነፃ የህክምና፣ የስነልቦና ምክር አግልግሎት እና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

በአጠቃላይ መንግስት በከባድ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የተጠረጠሩ ግለሰቦችን በፍጥነት ለፍትህ ማቅረቡ ሊመሰገን የሚገባው ተግባር ነው፡፡ይህ የፍርድ ሒደት መንግስት ከበቀል በፀዳ መልኩ ሕግን ብቻ መሠረት ያደረገ እንቅስቃሴ በማድርግ ላይ መሆኑን የሚያሳይበት፤ ዜጐች በፍርድ ቤቶች ላይ የተሸረሸረ እምነታቸውን የሚያድሱበት እና የሕግ ልዕልና የሚከበርበት የፍርድ ሒደት እንዲሆን ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

መግለጫውን በፒዲኤፍ እዚህ ያገኛሉ

ሰመጉ በአፍሪካ የሕዝቦችና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የታዛቢነት ቦታ አለው፤ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ፌዴሬሽን (FIDH) አባል፣ የዓለም ዓቀፍ ፀረ-ስቃይ ድርጅት (OMCT) አባል እና የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ሕብረት (DefendDefenders) መሥራች አባልም ነው፡፡

የራያ እና የወልቃይት የማንነት እና እራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄን አስመልክቶ ከሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) የተሰጠ መግለጫ

ጥቅምት 16 ቀን 2011 ዓ.ም

በትግራይ ክልል አላማጣ ከተማ የራያን ህዝብ የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ ይዘው ጥቅምት 11 ቀን 2011 ዓም ሰልፍ በወጡ ዜጐች ላይ የክልሉ ልዩ ኃይል በወሰደው የሃይል እርምጃ ቢያንስ 9 ሰዎች በጥይት ተመተው መገደላቸውን፤ 16 ወጣቶች በጥይት መቁሰላቸውን፤ እንዲሁም ከ50 በላይ ወጣቶች እየተደበደቡ ታፍነው መወሰዳቸውን ምንጮች ለሰመጉ አረጋግጠዋል፡፡ በተጨማሪም ከ500 በላይ የሚሆኑ የአላማጣ ወረዳ ወጣቶች ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለው በቆቦ ከተማ ተጠልለው እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡ ከተገደሉት ሰዎች መካከል፡

  1. ነጋሲ እዮብ
  2. ካሳ ንጉስ
  3. መሀመድ ዋከዬ
  4. ሞላ አብርሃም እንደሚገኙበት የሰመጉ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

ራያ ቀደም ሲል በወሎ ጠቅላይ ግዛት ውሰጥ የነበረ ሲሆን ከ1985 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ ትግራይ ክልል ተጠቃሎ በአሁኑ ሰዓት በትግራይ ክልል አስተዳደር ስር ይገኛል፡፡ ይህንን ተከትሎ ለበርካታ አመታት በቋንቋቸውና በባህላቸው የመታወቅ ብሎም የመጠቀም፣ የማዳበር እና የማስፋፋት ሕገ-መንግስታዊ መብታቸው እንደተጣሰ በአዲስ አበባ የሚገኙ የራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ ለሰመጉ አስረድቷል፡፡ የራያ ሕዝብ የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴዎች ለሰመጉ እንደገለፁት ከማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ እየተፈፀሙ ያሉ የመብት ጥሰቶችን ለጠቅላይ ሚንስትር ቢሮ እና ጉዳዩ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት በተደጋጋሚ ቢያሳውቁም መንግስት ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት በመንፈጉ ችግሩ ተባብሶ እዚህ ደረጃ ደርሷል፡፡

ራያ አላማጣ

 

የፌደራል መንግስት የራያ ህዝብ ያነሳውን ህገ- መንግስታዊ የማንነት ጥያቄ እና ከጥያቄው ጋር ተያይዞ እየተከሰቱ ያሉትን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች በሰከነ ሁኔታ ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን በተከተለ መንገድ እንዲፈታ ሰመጉ ይጠይቃል፡፡ በተጨማሪም መንግስት ከራያ ህዝብ የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ የዜጐችን በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነት እና የነፃነት መብቶች ላይ ጥሰት የፈፀሙ እና ያስፈፀሙ አካላትን አጣርቶ ለፍርድ እንዲያቀርብ ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

በሌላ በኩል የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ከዚህ ቀደም ”በኢ.ፌዲሪ ሕገ-መንግስት መሠረት የማንነት ጥያቄ በሚያነሱ ዜጐች ላይ የሚፈጸመው ግድያ፣ ሕገወጥ እስራት፣ አፍኖ መሠወር፣ ማፈናቀልና ንብረት መንጠቅ በአስቸኳይ ይቁም” በሚል ርዕስ 141ኛ ልዩ መግለጫውን ግንቦት 24 ቀን 2008 ዓም ማውጣቱ ይታወሳል፡፡ ሰመጉ በመግለጫው የመጀመሪያ ክፍል የአማራ ብሔረተኝነት የማንነት ጥያቄ በማንሳታቸው ምክንያት 34 የወልቃይት ተወላጆች መገደላቸውን፣ 93 ሰዎች ታፍነው የደረሱበት አለመታወቁን ጨምሮ በተለያዩ ሰዎች ላይ ድብደባ ማሠቃየት፣ ሕገ ወጥ እስራቶች መፈፀሙን እና የእርሻ መሬት፣ መኖሪያ ቤትና ንብረታቸውን መነጠቃቸውንና ዜጎች መፈናቀላቸውን ዘርዝሯል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የወልቃይትን ሕዝብ የማንነትና የታሪክ ጥያቄ ለማጥፋት የአካባቢውን ነባር የቦታ ሥያሜዎች በአዲስ ሥያሜዎች መቀየራቸውን የኮሚቴው አባላት መግለፃቸውን ጠቅሶ ሰመጉ በሪፖርቱ ይፋ ማውጣቱ ይታወሳል፡፡ ከ141ኛ ልዩ መግለጫ በኋላም የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ የአማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ በተለያዩ ጊዜያት በወልቃይት ሕዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ለሰመጉ ሲያመለክቱ ቆይተዋል፡፡

ጥቅምት 6 ቀን 2011 ዓ.ም የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ የአማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ለተለያዩ ለሚመለከታቸው የመንግስት ተቋማትና ለኤምባሲዎች የተነጠቀ የአማራ ማንነታችን እንዲመለስልን ለ6ኛ ጊዜ የቀረበ አቤቱታ በማለት ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡ ኮሚቴው ከ1974 ዓም ጀምሮ የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ግፍና በደል ሲፈፀምበት ቢቆይም ለሕዝቡ ጩኸት መንግስት የሚጠበቅበትን ምላሽ እንዳልሰጠ አስረድቷል፡፡ የሕዝቡን ጥያቄ ለማፈን እያጋጠሙ ያሉ ወቅታዊ ችግሮች ናቸው በማለት ኮሚቴው በአቤቱታው ላይ ከዘረዘራቸው ችግሮች መካከል፤

 

ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ኮሚቴ አባላትን በፀረ ሽብር ሕግ በመክሰስና በማሰር ከቆየን በኋላ መንግስት ለሰላም ሲል በወሰደው እርምጃ ከእስር የተፈታን ቢሆንም አሁንም የኮሚቴው አባላት በየሄዱበት እየታሰሩ ነው፤ ሌሎች አባላትም ወደ ቤታቸው እንዳይመለሱ ከፍተኛ በደል እየደረሰባቸዉ በስደት ላይ ይገኛሉ፤

ከዚህም በተጨማሪ በወልቃይት ጠገዴ የሚኖሩ ዜጐች በአማርኛ ቋንቋ እንዳይነጋገሩና የአማርኛ ሙዚቃ እንዳይሰሙ እየተከለከሉ ነው፤ ይህንን ትዕዛዝ ጥሶ የተገኘ ሰው እየተደበደበና እየታሰረ ይገኛል፤

ነሐሴ 16 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በወልቃይት ጠገዴ የሚገኙ ወጣቶችና እና የማንነት ጥያቄ የሚያቀርቡ አዛውንቶች እየተደበደቡና እየታሰሩ እንዲሁም ከአካባቢያቸዉ እንዲሰደዱ እየተደረገ ይገኛል፡፡

በተለይ በአሁኑ ሰዓት ጥያቄያችንን ለማዳፈን የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ:: በዚህም ምክንያት ሕይወታችንና እንደ ህዝብ የመቀጠል ህልውናችን  አደጋ ውስጥ ገብቷል በማለት የወልቃይት ህዝብ የማንነት ጠያቂ ኮሚቴ አባላት ለሰመጉ በአካል ቀርበው አመልክተዋል፡፡ በዚህም መሠረት የወልቃይት ጠገዴን ሕዝብ አካባቢውን ጥሎ እንዲሰደድ የተለያዩ ጫናዎች እየተፈፀሙባቸው እንደሚገኝና የመከላከያ ሃይልና የፌዴራል ፖሊስ በቦታው ተሰማርቶ ከተጋረጠብን ከፍተኛ የአደጋ ስጋት ሊጠብቀን ይገባል ብለዋል፡፡

ሰመጉ የፌዴራል መንግስት ለወልቃይት ህዝብ የማንነት ጥያቄ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር በአስቸኳይ ዘላቂ መፍትሄ እንዲሰጥ፤ እንዲሁም የሰው ህይወት ያጠፉ፣ አካል ያጎደሉና ንብረት ያወደሙ አካላትን በአስቸኳይ ለህግ እንዲያቀርብ፤ ለተጐጂዎች ተመጣጣኝ ካሳ እንዲከፈልና የተፈናቀሉ ሰዎችን መልሶ በማቋቋም ወደቀያቸው እንዲመልስ፤ ለደህንነታቸውም ዋስትና እንዲሰጥ አጥብቆ ይጠይቃል፡፡

በአጠቃላይ ባለፉት አመታት የራያ እና የወልቃይት  ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሌሎችም የማንነት እና እራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄን በስፋት ሲያቀርቡ መቆየታቸው ይታወቃል፡፡ ለእነዚህ የማንነት ጥያቄዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ምላሽ መስጠት አስቸጋሪ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ የሁሉንም የፖለቲካ አካላት እና የዜጎችን ገንቢ ተሳትፎ ማረጋገጥ ለሀገር አንድነት ወሳኝ መሆኑን ሰመጉ ይገነዘባል፡፡ በመሆኑም ለአመታት በአፈሙዝ ተዳፍነው የቆዩ ጥያቄዎችን በጥይት ሳይሆን በሕግ እና በስርዓት መፍታት ለዜጐች ሁለንተናዊ መብቶች መከበር ብቸኛው አማራጭ መሆኑን በመገንዘብ መንግስት ተገቢውን እርምጃ እንዲወስድ ሰመጉ ያሳስባል፡፡

በመጨረሻም፤ መንግስት ለሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር እንዲሁም ለህግ የበላይነትና የፍትሕ ስርዓቱን ለማሻሻል የገባውን ቃል እንዲተገብርና የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲ መብቶችን እንዲያከብርና እንዲያስከብር ሰመጉ በዚህ አጋጣሚ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

መግለጫውን በፒዲኤፍ እዚህ ያገኛሉ

 

ሰመጉ በአፍሪካ የሕዝቦችና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የታዛቢነት ቦታ አለው፤ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ፌዴሬሽን (FIDH) አባል፣ የዓለም ዓቀፍ ፀረ-ስቃይ ድርጅት (OMCT) አባል እና የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ሕብረት (DefendDefenders) መሥራች አባልም ነው፡፡

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልና በአጎራባች አካባቢዎች እየደረሰ ያለው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች በአስቸኳይ ይቁም! ለብሔር ተኮር ጥቃቶች እና ግጭቶች ሕጋዊና ፖለቲካዊ መፍትሔ ይሰጣቸው!!

መስከረም 25 ቀን 2011 ዓ.ም

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ከዚህ ቀደም በቤኒሻንጉልና ኦሮሚያ ክልል አጎራባች አካባቢዎች ብሔርን መሰረት ያደረጉ ግጭቶች ያስከተሉትን ከፍተኛ የሆነ የህይወትና የንብረት ውድመት በአካባቢው በመገኘት በባለሙያዎቹ አማካኝነት በማጣራት የደረሠውን የጉዳት መጠን እና ሊወሰዱ የሚገባቸውን እርምጃዎች ይፋ አድርጓል፡፡ ለትውስታ ያህል ሐምሌ 10 ቀን 2000 ዓ.ም የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ በኢትዮ ጵ ያ በሚል ርዕስ ባወጣው 31ኛ መደበኛ መግለጫ በጉሙዝና ኦሮሞ ብሔረሠብ ዜጐች መካከል በ 09/09/2000 ዓ.ም በተፈጠረ ግጭት 99 (ዘጠና ዘጠኝ) ሰዎች መገደላቸውን፣ በርካታ ሰዎች መቁሰላቸውን፣ 108 የሚሆኑ መኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውን፣ እንዲሁም ከ27‚000 (ሀያ ሰባት ሺ) በላይ ህዝብ መፈናቀሉን በማስረጃ አስደግፎ ይፋ ማድረጉ ይታውሳል፡፡ በመግለጫውም መንግስት በአስቸኳይ ዘላቂና የማያዳግም መፍትሄ እንዲሰጥ ቢያቀርብም መንግስት ለሰመጉ ጥሪ ትኩረት ባለመስጠቱ ዛሬም ብሔርን መሰረት ያደረገ ጥቃትና ግጭት ሊፈፀም ችሏል፡፡
መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ከማሽ ዞን አመራሮች ከምዕራብ ኦሮሚያ አስተዳደር ጥምር ኮሚቴ ጋር የነበራቸውን ስብሰባ አጠናቀው ሲመለሱ ከማሺ ወረዳ ላይ ማንነታቸው ባልታወቁ ታጣቂዎች በተሰነዘረባቸው ጥቃት አራት አመራሮች በመገደላቸው ለግጭቱ መቀስቀስ ምክንያት ሆኗል። ግድያውን ተከትሎም በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ከማሽ ዞን በሎይ ጅጋንፎ ወረዳ ዳለቻ እና ታንኮና በተባሉ ቀበሌዎች ችግሩ በዋናነት ተፈጥሯል፡፡ ሰመጉ እስካሁን ባሰባሰበው መረጃ መሠረት ከጥቃቱ ጋር በተያያዘ ከ 90,000 (ከዘጠና ሺ) በላይ ዜጐች ቤት ንብረታቸውን ጥለው ወደ አጎራባች አካባቢዎች ተፈናቅለዋል፣ ከ200 በላይ ቤቶች ተቃጥለዋል፣ ከ74 በላይ ክቡር የሰው ህይወት ጠፍቷል፡፡ እንዲሁም በበርካቶች ላይ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል በርካታ ሰዎችም የደረሱበት ያልታወቀ ሲሆን በርካታ ቁስለኞችም በነቀምቴ ሆስፒታል በመታከም ላይ ይገኛሉ። መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሟቾቹ ውስጥ በርካታ የፀጥታ ሀይሎችም ይገኙበታል፡፡
ግድያና ማቁሰል

 ከሀገሎ ሜጢና አካባቢው ሸሽተው በምዕራብ ወለጋ ነጆ ከተማ ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ ተፈናቃዮች እንደገለፁት በቤኒሻንጉል ክልል አንገር ሜጢ ከተማ ውስጥ 13 ሰዎች ተገድለዋል፤ ከእነዚህም ውስጥ ሁኔታውን ለማረጋጋት ሲጥሩ የነበሩ 3 አድማ በታኝ ፖሊሶችና 2 ሴቶች ይገኙበታል፤

 ከከማሼና አካባቢው ተፈናቅለው በምዕራብ ወለጋ ቢላ ከተማ ውስጥ የተጠለሉ ተፈናቃዮች እንደገለፁት በከማሼና አካባቢው 31 ሰዎች ተገድለዋል፤ ከእነዚህም ውስጥ 4 ሴቶችና 3 ፖሊሶች ይገኙበታል፤

 ከሶጌ፣ በሎ አካባቢዎች ተፈናቅለው በምስራቅ ወለጋ ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ ተፈናቃዮች እንደገለፁት በሶጌ፣ በሎና አካባቢው ውስጥ 30 ሰዎች መገደላቸውንና ከዚህም ውስጥ 13 ፖሊሶች ይገኙበታል፤

 የቆሰሉ ሰዎችን በሚመለከት ቁጥራቸው በርካታ የሆኑት በነቀምቴ ሆስፒታል፣ በወለጋ ዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታልና በተለያዩ የግል ሆስፒታሎችና ክሊኒኮች ውስጥ እየታከሙ እንደሚገኙ ለሰመጉ በአካባቢው የሚገኙ ታማኝ ምንጮች አስረድተዋል፡፡

ሰመጉ በቅርብ ግዜ ውስጥ ከላይ የተጠቀሱትን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችና በእስካሁኑ የመረጃ አሰባሰብ ያልተደረሰባቸውን በሁለቱም ወገኖች መካከል የደረሰውን ሰብዓዊና ኢኮኖሚያዊ ውድመት እንዲሁም የችግሩን መነሻ ምክንያቶች በስፋትና በጥልቀት በመመርመር በመግለጫ ይፋ እንደሚያደርግ ከወዲሁ ይገልፃል፡፡

ማፈናቀል

በቤኒሻንጉል ክልል ነዋሪ የነበሩ ዜጐች በግጭቱ ምክንያት የመኖሪያ አካባቢያቸውን በመልቀቅ በምስራቅ ወለጋ በ13 ጣቢያዎች በዲጋ ወረዳ አርጆ ጉደቱ፣ ላሲጋ፣ ጊዳ ኪረሙ፣ ጊቶ ጊዳ፣ በተለያዩ ቦታዎች፣ በነቀምት ከተማ ወለጋ ዩኒቨርስቲ፣ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ፣ የነርሶች ማሰልጠኛ፣ 05 ቀበሌ፣ 07 ቀበሌ፣ ዳርጌ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት፣ ዳንዲቦሩ ኮሌጅ፣ በ 9 መጠለያ ቦታዎች፤ እንዲሁም በምዕራብ ወለጋ ነጆ ወረዳ አስተዳደር አዳራሽ ነጆ ደር መጂ ወረዳ ቢላ ከተማ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ተጠልለው ይገኛሉ። በአጠቃላይ ከቤኒሻንጉል ክልል ተፈናቅለው በምዕራብና ምስራቅ ወለጋ ተጠልለው የሚገኙ ተፈናቃዮችም ከ90,000 በላይ እንደደረሰ ሰመጉ ከአካባቢዎቹ ያሰባሰባቸው መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ሰመጉ ከአካባቢው ያሰባሰባቸው መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ግጭቱ አሁንም ያልቆመ ሲሆን በርካታ ተፈናቃዮች በየጫካው ተበትነው ይገኛሉ፤ የተጠፋፉ ቤተሠቦችንም ማገናኘት አልተቻለም፡፡ የምስራቅ ወለጋ ዞን አስተዳደር ባሁኑ ሰዓት የተፈናቃዮች ቁጥር ከአቅማቸውና ከቁጥጥራቸው በላይ በመሆኑ የሁሉም አካላት እርብርብ እንደሚያስፈልግ ለሰመጉ ገልፀዋል፡፡ በዚህ አጋጣሚም መንግስት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ለተጎጂዎችም የምግብ፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የአልባሳትና የመድሀኒት አቅርቦት በአስቸኳይ እንዲያቀርብ ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

ብሔርን መነሻ ባደረጉ ጥቃቶች እና ግጭቶች ምክንያት ባለፉት አምስት ወራት ብቻ በተለያዩ ክልሎች ከሁለት ሚሊዮን በላይ ዜጐች ከመኖሪያቸው ተፈናቅለዋል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተገድለዋል፤ በርካቶች ቆስለዋል፡፡ ከዚህም በላይ ዜጐች በገዛ ሐገራቸው በሰላም ወጥቶ የመግባት ዋስትናቸው ጥያቄ ውስጥ ወድቋል፡፡ መንግስት የዜጐችን በሕይወት የመኖር፣ በሐገሪቱ በፈለጉበት አካባቢ ተንቀሳቅሶ ኑሮን የመመስረትና ንብረት የማፍራት ሕገመንግስታዊ መብቶች እንዲጠብቅ እና እንዲያስከብር ሰመጉ ጥሪውን በድጋሚ ያቀርባል፡፡ በተጨማሪም መንግስት በሐገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች እየተፈፀሙ ላሉት ጥቃቶች እና ግጭቶች ተገቢዉን ትኩረት በመስጠት እየተባባሰ የመጣውን ችግር በዘላቂነት ለመቆጣጠር ሕብረተሰቡን እና የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎችን ያማከለ፣ ዘላቂ፣ ሕጋዊ እና ፖለቲካዊ መፍትሔ እንዲወስድ ሠመጉ ያሳስባል፡፡

ጋዜጣዊ መግለጫውን በፒዲኤፍ ያውርዱ

 

የ ሰ ብ ዓ ዊ መ ብ ቶ ች ጉ ባ ዔ ( ሰ መ ጉ ) ፣ የ ቀ ድ ሞ ው የ ኢ ት ዮ ጵ ያ ሰ ብ ዓ ዊ መ ብ ቶ ች ጉ ባ ዔ ( ኢ ሰ መ ጉ ) በኢትዮጵያ የሽግግር ወቅት ቻርተር አንቀጽ 1( ሀ ) እና በኢትዮጵያ ፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር ከ 404 – 482 በተጻፉት ድንጋጌዎች መሠረት መስከረም 29 ቀን 1984 ዓ . ም . በአባላት የተመሠረተ የመጀመሪያው መንግሥታዊ ያልሆነ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ነው፡፡

በአዲስ አበባ ለተፈፀመው ጅምላ እሥራት መንግስት በቂ ማብራሪያ ሊሰጥበት ይገባል – መስከረም 18 ቀን 2011 ዓ.ም

መስከረም 18 ቀን 2011 ዓ.ም

ሰሞኑን በአዲስ አበባ የተካሔደው ጅምላ እስር ከመንግስት ሙሉ ማብራሪያ ሊሰጥበት ይገባል፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር በሰጡት መግለጫ ባለፈው ሳምንት በመዲናችን በተካሔደው የጅምላ እስር በከተማዋ በነበረው (ሁከት) ቀጥተኛ ተሳትፎ አድርገዋል ያላቸውን 1,204 ዜጉችን ጨምሮ፤ ከጫት ቤት፣ ከሺሻ ቤትና ከቁማር ቤት በገፍ ያፈሳቸውን በአጠቃላይ ወደ ሶስት ሺህ የሚደርሱ ዜጐችን ማሰሩን ገልፀዋል።

ምንም እንኳን ፖሊስ ከተማዋን ለማረጋጋት እርምጃ መውሰዱ ተገቢ ቢሆንም ከሕግ አግባብ ውጪ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መጠነ_ሰፊ እስር መፈፀሙ፣ ጅምላ እስራቱ ሠላማዊ ዜጐችንም ጭምር ዒላማ ማድረጉ፣ ጥቂት የማይባሉ ታሳሪዎች ላይ ፖሊስ ድብደባ መፈፀሙ፣ ብሎም ዘላቂ የአካል ጉዳት ማድረሱ፣ በሕግ ወንጀል እንደሆነ በግልፅ ባልተደነገጉ ሥፍራዎች ያገኛቸውን ዜጐች ማሠሩ፣ ከሕግ አግባብ ውጪ ከምሽቱ 12 ሰዓት በኋላ እስራቶቹ መፈፀማቸው፣ እንዲሁም ሠላማዊውን ሕዝብ ጭንቀት ውስጥ በከተተ መልኩ ግልፀኝነት በጐደለው ሁኔታ የጅምላ እስሩን መነሻ ምክንያት እና የታሳሪዎችን እጣ ፈንታ በፍጥነት ለሕዝብ ይፋ አለማድረጉ የፖሊስን እርምጃ ሕጋዊነት ጥያቄ ውስጥ የሚጥል ነው።

ሰመጉ ያነጋገራቸው የእስሩ ገፈት የቀመሱ ዜጐች ፖሊስ በምርመራ ወቅት የተቀናቃኝ ፓርቲዎች አመራሮች ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ የአቀባበል ዝግጅቱን ለምን አስተባበራችሁ፣ ለምን የፓርቲዎቹ ደጋፊ ሆናችሁ የሚሉና ተመሳሳይ የምርመራ ጥያቄዎች እንደቀረቡላቸው ለሰመጉ አስረድተዋል፡፡ እነዚህን ጥያቄዎችን እና ከቡራዩ ለተፈናቀሉ ዜጎች ሰብዓዊ እርዳታ ለማድረግ ሲያስተባብሩ የነበሩ የአዲስ አበባ ወጣቶች በብዛት መታሠራቸውን ስንመለከት፣ ፖሊስ የሰጠውን “ሁከትን የማረጋጋት“ ምክንያት ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ አስገብቶታል፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በሁከቱ ቀጥተኛ ተሳታፊ ነበሩ ያላቸውን 1,204 ዜጐች ለተሃድሶ ስልጠና በሚል ምክንያት ወደ ጦላይ ወታደራዊ ማሠልጠኛ ካምፕ መውሰዱንም አረጋግጧል፡፡ ወንጀል ፈፅመዋል ተብለው የተያዙ ሰዎች በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት መቅረብ እንዳለባቸው በግልፅ ቢደነግግም ፖሊስ ይህንን የታሳሪዎች ህገ-መንግስታዊ መብት በመጣስ ካለፍርድ እና ገደቡ ለማይታወቅ ግዜ ታሳሪዎችን ወድ ወታደራዊ ካምፕ ወሰዷል፡፡ ፖሊስ ታሳሪዎቹን በመደበኛ ፖሊስ ጣቢያዎች ለማቆየት ያልቻለበትንም ምክንያት ግልፅ አላደረገም፡፡ ይህ የፖሊስ ድርጊት የዜጐችን ሕገ መንግስታዊ መብት በግልፅ የጣሰ በመሆኑ ከሕግ አግባብ ውጪ የተያዙ፣ ክስ ሳይቀርብባቸው ወይም ሳይፈረድባችው የታሰሩ ዜጐች እንዲፈቱ ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

ሀገሪቱ በአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ውስጥ በነበረችበት ወቅት በተለያዩ ወታደራዊ ካምፖች ታስረው የነበሩ ዜጐች ይደርስባቸው የነበረውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ትውስታ ከአእምሮ ባልጠፋበት በዚህ ወቅት ለስልጠና በሚል ሠበብ መንግስት ዜጐችን ወደ ወታደራዊ ካምፕ ማጋዙ ለሌላ ዙር መጠነ-ሰፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳያጋልጣቸው ሰመጉ ይሰጋል፡፡ በመሆኑም በሁከት እና በግርግር ውስጥ ተሳትፈዋል በሚል በሕግ ጥላ ስር የሚገኙ ዜጐች ሰብዓዊ መብታችውን በጠበቀ መልኩ የመያዝ መብታችው እንዲከበር፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በወዳጀቻቸው እና በሕግ አማካሪዎቻቸው የመጐብኘት መብታቸው እንዲጠበቅላቸው፤ እንዲሁም ክስ ያልተመሠረተባቸው ዜጐች በፍጥነት እንዲለቀቁ ሰመጉ ይጠይቃል፡፡

መግለጫውን በፒዲኤፍ እዚህ ያገኛሉ።

 

የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ)፣ የቀድሞው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) በኢትዮጵያ የሽግግር ወቅት ቻርተር አንቀጽ 1(ሀ) እና በኢትዮጵያ ፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር ከ404-482 በተጻፉት ድንጋጌዎች መሠረት መስከረም 29 ቀን 1984 ዓ.ም. በአባላት የተመሠረተ የመጀመሪያው መንግሥታዊ ያልሆነ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ነው፡፡

 

በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች እየተከሰቱ ያሉ ብሔር-ተኮር ግጭቶችን እና በቡድን የተደረጁ ኃይሎች እየፈፀሟቸው ያሉትን ከባድ ጥቃቶች መንግስት በአስቸኳይ ሊያስቆም ይገባል።

መስከ ረም 8 ቀን 2011 ዓ .ም

የጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ አመራር ወደ ሥልጣን ከመጣ ጀምሮ ሀገሪቱ በሁለት ተጻራሪ ሁነቶች ውስጥ እያለፈች
ትገኛለች። በአንድ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የወሰዷቸው መልካም ርምጃዎች ሀገሪቱ ተጋርጦባት የነበረውን ከፍተኛ ስጋት
ለጊዜውም ቢሆን ያስታገሰ፣ የዜጐች ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ያበረታታ፣ እንዲሁም የዲሞክራሲን ጭላንጭል
የፈነጠቀ ነው። በአንፃሩ በራሳቸው በጠ/ሚኒንስትር አብይ ላይ የተቃጣውን የግድያ ሙከራ ጨምሮ፣ በተለያዩ አካባቢዎች
ህገወጥ ግድያዎች፣ ዘርን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች እና ግጭቶች፣ የመንጋ “ፍትሕ” እና ስርዓት አልበኝነት በተለያዩ የሐገሪቱ
ክፍሎች እየተንሰራፉና ከዕለት ወደ ዕለት ከቁጥጥር ውጪ እየሆኑ ነው። በአደባባይ ከተፈፀሙ ወንጀሎች እና የሰብዓዊ
መብቶች ጥሰቶች መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፤

  • በደቡብ ክልል ሸካ ዞን ቴፒ ከተማ በ09/12/10 ጀምሮ ብሄርን መሰረት ያደረገ ግጭት ተከስቶ 3 ሰዎች ተገድለዋል፣
    በርካታ ንብረት ተዘርፏል፣ ቤት ንብረትም ተቃጥሏል፡፡ የመከላከያ ሰራዊት ጣልቃ በመግባት ግጭቱን ያረጋጋ ቢሆንም ዳግም ከ15/12/10 ጀምሮ ግጭቱ እንደ አዲስ በመቀስቀሱ ሌሎች 2 ሰዎች ተገድለዋል፡፡
  • በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ባሌ ዞን በጎባ ከተማና አካባቢው ከሀምሌ 13-16 2010 ዓ.ም. የተደራጁ ወጣቶች በፈፀሙት ጥቃት የ10 ሰላማዊ ሰዎች ህይወት ጠፍቷል፣
  • ደቡብ ክልል ጋሞ ጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ የአካባቢው ህዝብ በሐምሌ 12 /2010 ዓ.ም. ሰላማዊ ሰልፍ አድርጎ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱለት ጠይቋል፡፡ ከዚሁ ሠልፍ ጋር በተያያዘ በተነሳ ረብሻ ወጣቶች የመንግስትና የህዝብ ንብረት ላይ ውድመት አድርሰዋል፡፡ በክልሉ በየም ልዩ ወረዳ ሀምሌ 15/2010 ለተመሳሳይ ጥያቄ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣታቸውን ተከትሎ በተከሰተ ግጭት 6 ሰዎች ተገድለዋል፣ በርካታ ንብረትም ወድሟል፣ ደቡብ ክልል ዳውሮ ዞን ተርጫ ከተማ ከነሀሴ 5-6 2010 ዓ.ም. በተደረገ ሰላማዊ ሰልፍ የመልካም አስተዳደርና የተለያዩ ጥያቄዎችን ጠይቋል በዚሁም እለት በተነሳ ግጭት 5 ሰዎች ተገድለዋል እንዲሁም ንብረት ወድሟል፣
  • በሻሸመኔ ከተማ በ6/12/2010 ዓ.ም. የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ አመራሮችን ለመቀበል በርካታ ህዝብ ወጥቶ ባለበት “ፈንጅ የጫነ መኪና መጣ” ተብሎ በተፈጠረ ግርግር 3 ሰዎች ተረጋግጠው ህይወታቸው ሲያልፍ፣ አንድ ሰው “ቦንብይዘሀል” ተብሎ በአሰቃቂና ኢሰብዓዊ በሆነ ሁኔታ ተቀጥቅጦ ተገድሏል፣ አስከሬኑም አደባባይ ላይ ተዘቅዝቆ
    ተሰቅሏል፤
  • ከሀምሌ 28-29 2010 ዓ.ም በሶማሌ ክልል በተለያዩ ከተሞች በተለይም ጅግጅጋ፣ ዋርዴር፣ ጎዴ፣ ደጋሀቡር፣ ፊቅ፣
    ቀላፎ እንዲሁም ድሬዳዋ ውስጥ ብሄርን መሰረት አድርጎ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት በተፈፀመ የተደራጀ ሰፊ ጥቃት
    ከ100 በላይ የሰው ህይወት ጠፍቷል፣ በበርካታ ሰዎች ከባድ የአካል ጉዳት ደርሷል፣ 9 አብያተ ክርስቲያናት
    ተቃጥለዋል፣ በርካታ መኖሪያ ቤቶችና ንግድ ቤቶች ላይ ዝርፍያና ቃጠሎ ተፈጽሟል፤ከዚህ ጋር በተያያዘም በድሬዳዋ
    14 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፤
  • በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ሀረርጌ ዞን በመዩ ሙለቱ ወረዳ ነሀሴ 13 2010 ዓ.ም ሮጌ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ተብሎ
    በሚጠራ አካባቢ የሶማሌ ልዩ ሀይል 31 የሚሆኑ ሰዎችን በጥይት ገድለዋል፤
  • ነሀሴ 18 2010 ዓ.ም በድሬዳዋ ከተማ በፌዴራል ማረሚያ ቤት የሚገኙ ታራሚዎች ከይቅርታ አዋጅ አተገባበር ጋር
    በተያያዘ ባስነሱት አመፅ የ1 ታሳሪ ህይወት ሲያልፍ 3 የፖሊስ አባላት እና 3 ታራሚዎች ላይ ከባድ የአካል ጉዳት
    ደርሷል፤
  • የአማራ የማንነት ጥያቄ አንስታችኋል ተብለው 85 ሰዎች ኮረም ላይ የታሰሩ ሲሆን ሐምሌ 11 እና 18 ቀን 2010
    ዓም ዋጃ ላይ 3 ሰዎች፣ እንዲሁም ነሐሴ 13 ቀን 2010 ዓም ኮረም ላይ 1 ወጣት ተገድሏል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ ከአላማጣ ወረዳ ከዋጃ፣ ጥሙጋ፣ ሰሌን ውሃ፣ ቢትሙ፣ ሀርሌ፣ አየር ማረፊያ እና በአጐራባች ቀበሌዎች ነሐሴ 285 ሰዎች ተፈናቅለው ራያ ቆቦ ወረዳ አልማ ትምህርት ቤት ውስጥ ተጠልለው ይገኛሉ።
  • በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን በመሰንቃና በማረቆ ማህበረሰብ መካከል የቀበሌ ይገባኛል ጥያቄ ቀርቦ ለረዥም ጊዜ መልስ
    ሳይሰጠው በመቆየቱ መስከረም 03 ቀን 2011 ዓም ከቆሼ ከተማ የጀመረው ግጭት እንሴኖና ቡታጅራ ድረስ ተስፋፍቶ እንሴኖ ላይ 3 ሰዎች ቡታጅራ ላይ 8 ሰዎች ተገድለዋል፡፡ በርካታ የመንግስት ተቋማት እና የግለሰቦች ንብረቶች ላይ ውድመት ደርሷል፡፡

ለዘመናት በበርካታ ችግሮች ተወጥራ የነበረችው ኢትዮጵያ በከፍተኛ መስዋዕትነት የተገኘውን የዲሞክራሲ ጭላንጭል ሊጨልም ስር የሰደዱ ችግሮች እየተገዳደሩት ይገኛል። የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች በበርካታ አጋጣሚዎች የተፈጠሩ ችግሮችን በፍጥነት ለመቆጣጠርም ሆነ ሊፈጠሩ የሚችሉ ችግሮችን ቀድሞ በማጥናት ችግሮቹ ከመፈጠራቸው በፊት የመከላከል እርምጃ ሊወስድ አልቻለም። ለአመታት በውጭ ሃገራት የነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ወደ ሃገራቸው መመለሳቸውን ተከትሎ የአቀባበል ስነ ስርዓቶቹን በተገቢው መንገድ ለመቆጣጠር በመንግስት በኩል የተደረገው ቅድመ_ዝግጅት ፍፁም ደካማ ሆኖ ታይቷል። በተለይም የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አመራሮችን ለመቀበል ደጋፊዎቻቸው ያደረጉት እንቅስቃሴ እና ይህን ተከትሎ በመዲናችን በተለያዩ አካባቢዎች ከባንዲራ ጋር በተያያዘ የተነሱ ግጭቶች ተከትሎ ሊመጣ የሚችለው አደጋ በግልፅ የሚታይ የነበረ ቢሆንም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት እና የፌዴራል መንግስት በቂ ትኩረት ሊሰጡት አልቻሉም። መስከረም 05 ቀን 2011 ዓም የኦነግ አመራሮችን ለመቀበል የተዘጋጀው ፕሮግራም በሰላም መጠናቀቁ የሚደነቅ ቢሆንም ምሽቱን በቡራዩ እና አካባቢው የሚኖሩ ንፁሃን ላይ የተፈፀመውን ጥቃት የፌዴራልም ሆነ የኦሮሚያ ክልል መንግስታት ለመቆጣጠር ባለመቻላቸው ዜጐች በአሰቃቂ ሁኔታ የዘር-ተኮር ጥቃቱ ሠለባ እንዲሆኑ አስገድዷል።

ውጤቶች ናቸው፡፡ ለረዥም ግዜ በተለይም በማህበራዊ ሚዲያው የሚሰራጩ ፀብ ቀስቃሽ የጥላቻ ንግግሮች ዜጐችን ወደ
አልተፈለገ መስመር እየገፋ መሆኑ በግልፅ ቢታይም መንግስት ተገቢውን እርምጃ በወቅቱ ሊወስድ አልቻለም። በዚህም ባለፉት ቀናት ቡራዩ፣ በአሸዋ ሜዳ፣ ከታ እና አካባቢው የተፈፀመ ዘር ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መንግስት በገለፀው መሠረት 25 ዜጐች ክቡር ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ በተጨማሪም ቁጥራቸው በውል ላልታወቀ ሴቶችና ህጻናት መደፈር፣ ለበርካቶች አካል ጉዳት እና ከስምንት ሺህ በላይ ንፁሃን ከቤት ንብረት መፈናቀል አስከትሏል። ይፋ በመውጣት ላይ የሚገኙትና ጥቃቱን የሚያሳዩት ምስሎች የድርጊቱን አፈፃፀም ጭካኔ ብቻ ሳይሆን በቡድን የተደራጁ ኃይሎች እየተጓዙበት ያለውን አቅጣጫ ፍፁም አደገኝነት የሚያመለክቱ ናቸው።

ይህንን ተከትሎ በንፁሃን ዜጐች ላይ በተፈጸመው ጥቃት እና በፌዴራል መንግስት ዳተኝነት የተቆጡ የአዲስ አበባ ዜጐችም
ብሶታቸውን ለማሰማት በብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ እና በአደባባዮች መስከረም 07 ቀን 2011 ዓም ተገኝተዋል። ይሁን እንጂ ሕዝባዊው ተቃውሞው ሠላማዊ የነበረ ቢሆንም የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የሃይል እርምጃ እስካሁን ድረስ ቢያንስ የአምስት ሠልፈኞች ህይወት ማለፉን ሰመጉ አረጋግጧል። በተያያዘም በዚሁ ዕለት በአርባ ምንጭ ከተማ በተደረገ ተመሳሳይ ህዝባዊ ተቃውሞ ስምንት ስዎች በጥይት የተመቱ ሲሆን የአንደኛው ግለሰብ ሕይወት ማለፉን ለሰመጉ የደረሰው መረጃ ያመለክታል፡፡ (ሰመጉ ከመስከረም 05 ቀን 2011 ዓም ጀምሮ በቡራዩ እና አካባቢው እንዲሁም መስከረም 07 ቀን 2011 ዓም በአዲስ አበባ እና በአርባ ምንጭ ከሠላማዊ ሠልፍ ላይ የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የሀይል እርምጃ የደረሰውን የህይወት መጥፋት፣ የአካል ጉዳት እና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን አጣርቶ ይፋ እንደሚያደርግ ከወዲሁ ይገልፃል)

የዜጐችን በሕይወት የመኖር መብት፣ የአካል ደህንነት መብት፣ በመላ ሀገሪቱ ተንቀሳቅሶ የመኖር፣ የመስራትና ንብረት
የማፍራት መብትን የማክበር እና የመጠበቅ ቀዳሚ ግዴታ የተጣለበት መንግስት ይህንን የዜጐች ሰብዓዊ መብት በማስከበር፣ ህገወጥነትን እና ስርዓት አልበኝነተን በመቆጣጠር በኩል ከፍተኛ የሆነ ቸልተኝነት አሳይቷል። ይህ ህዝባዊ ቁጣ ፈጣን ምላሽ ካላገኘ ፍፁም ወደ ሆነ ስርዓት አልበኝነት ላለመሸጋገሩ ምንም አይነት ዋስትና የለም።

በአጠቃላይ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በተለያዩ ስያሜዎች ዛሬ ላለንበት ጅምር የዴሞክራሲ ስርዓት ክቡር ሕይወታቸውን
ሰውተው ያደረሱን ወጣቶች ለዘላቂ ሠላም ጠቃሚ ከመሆኑ አንፃር ወደ ህጋዊ አደረጃጀት እንዲገቡ ተደርጐ የተጠያቂነት
አሠራር እንዲኖር መንግስት ተገቢዉን እርምጃ ሊወስድ ይገባል፡፡ በተጨማሪም የፌዴራል መንግስት የዜጐችን በህይወት
የመኖር፣ የአካል ደህንነት እና በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል በሙሉ ነጻነት የመንቀሳቀስ መብት በአፋጣኝ እንዲያስከብር፣
የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈጻሚዎች እና አስፈጻሚዎች ለሕግ እንዲያቅርብ፣ የሕግ የበላይነትን እንዲያሰፍን እና በአስቸኳይ
ሁሉን አቀፍ መፍትሔ እንዲፈልግ ሠመጉ ጥሪዉን ያቀርባል፡፡

መግለጫውን በፒዲኤፍ እዚህ ያገኛሉ።